Yakob's Point of Views and News, Ethiopian politics and News, Cultures, Musics etc

Sunday, June 30, 2013

የፕሬዚደንት ኦባማ የደቡብ አፍሪቃ ጉብኝት

አፍሪቃ

የፕሬዚደንት ኦባማ የደቡብ አፍሪቃ ጉብኝት

በሴኔጋል የሁለት ቀናት ይፋ ጉብኝት ያጠናቀቁት የዩኤስ አሜሪካ ፕሬዚደንት ባራክ ኦባማ ትናንት ምሽት ደቡብ አፍሪቃ ገብተዋል። ይሁንና፣ የቀድሞው የደቡብ አፍሪቃ ፕሬዚደንት ኔልሰን ማንዴላ በጠና የታመሙበት ሁኔታ በፕሬዚደንት ኦባማ ጉብኝት ላይ ጥላ አጥሎበታል።
ምንም እንኳን የደቡብ አፍሪቃ ፖለቲከኞች የሀገራቸው እና የዩኤስ አሜሪካ የጋራ ግንኙነትን ለማጉላት ቢሞክሩም፣ ደቡብ አፍሪቃውያን በወቅቱ የሚያሳስባቸው የብሔራዊው ውድ እና ጀግና ኔልሰን ማንዴላ ጤንነት ብቻ ነው።
« የማንዴላ ምግባር ፣ ቆራጥ ሰዎች፣ በጎ ፈቃድ ያላቸው እና ለትልቅ ዓላማ የተነሱ ሰዎች ባንድነት በሚንቀሳቀሱበት ጊዜ ፣ በዓለም ምን ሊሰራ እንደሚችል በግልጽ አሳይቶኛል። በእርግጥ በዚህ ቅፅበት ሀሳባችና እና ፀሎታችን ከደቡብ አፍሪቃ ሕዝብ እና በተለይም ከማንዴላ ቤተሰቦች ጋ ነው። »
ፕሬዚደንት ኦባማ በሴኔጋል ጉብኝታቸው ወቅት የቀድሞውን የደቡብ አፍሪቃ ፕሬዚደንት ኔልሰን ማንዴላን « የዓለም ጀግና» በሚል ሲያሞግሱዋቸው፣ ባልተቤታቸው ምሸል ኦባማ ደግሞ በመዲናይቱ ዳካር አንድ ትምህርት ቤት በጎበኙበት ጊዜ ተማሪዎቹ ራሳቸው አንድ ቀን አኩሪ ታሪክ ተተው ማለፍ እንዲችሉ የማንዴላን ምግባር ሁሌ እንዲያስታውሱ ጥሪ አሰምተዋል።
ያም ሆነ ይህ ግን የፕሬዚደንት ባራክ ኦባማ በአፍሪቃ ጠንካራ የኤኮኖሚ ኃያል መንግሥት ደቡብ አፍሪቃ የሚያካሂዱት ብዙ የተጠበቀው ጉብኝታቸው ያን ያህል የሕዝቡን ትኩረት ሳያገኝ ሊያልፍ የሚችልበት ስጋት ተደቅኖበታል። በተለያ ግዙፉ የፀጥታ ጥበቃ ጉዳይ ደቡብ አፍሪቃውያንን ብዙ እያነጋገረ ነው። በተለይ የዩኤስ አሜሪካ ጦር ብላክ ሆክ ሄሊኮፕተር በጆሀንስበረገ ከተማ ዝቅ ብሎ ሲበር ከታየ በኋላ አንድ ደቡብ አፍሪቃዊ አሜሪካውያን ሀገሪቱን ሊቆጣጠሩ ነው እንዴ ሲል በትዊተር አጠያይቋል። « ዘ ስታር» የተሰኘው የሀገሪቱ ጋዜጣ ደግሞ ከኦባማ ይበልጥ ጆርጅ ዳብልዩ ቡሽ በአፍሪቃ የሚታይ ነገር ሰርተዋል ሲል ጽፏል።
ይሁን እንጂ፣ የኦባማ ጉብኝት ግዙፍ የስራ አጥነት ችግር ለተደቀነባት ዴሞክራሲያዊቱ ደቡብ አፍሪቃ ከፍተኛ ትርጓሜ መያዙን የሀገሪቱ ፕሬዚደንት ጀኮብ ዙማ ብቻ ሳይሆኑ ሚንስትሮቻቸው ሳይቀሩ ተናግረዋል። ከዋነኞቹ የደቡብ አፍሪቃ የንግድ ሸሪኮች መካከል ዩኤስ አሜሪካ አንዷ ስትሆን፣ በደቡብ አፍሪቃ የሚገኙት 600 አዩኤስ አሜሪካ ተቋማት በሀ,ገሪቱ 120,000 የስራ ቦታ ፈጥረዋል። ዩኤስ በ 2010 ዓም በደቡብ አፍሪቃ ያንቀሳቀሰችው ቀጥተኛ ወረት 6,5 ቢልዮን ዶላር ነበር።

የቀድሞው የዩኤስ አሜሪካ ፕሬዚደንት ቢል ክሊንተን ለአፍሪቃ ባስተዋወቁት አጎዋ በተባለው ልዩ የንግድ ስምምነት መሠረት ደቡብ አፍሪቃ ወደ ዩኤስ አሜሪካ በንግድ ከምትልከው ዕቃና ምርት፣ በተለይ ጨርቃ ጨርቅ መካከል፣ 90% በቅናሽ ወይም ካለቀረጥ ይገባል። ደቡብ አፍሪቃ እና ዩኤስ አሜሪካ ለደቡብ አፍሪቃ ተጨማሪ የተመቻቸ የንግድ ሁኔታ የሚፈጥረውን በእንግሊዝኛ ምሕፃሩ ቲፋ በመባል የሚታወቀውን የንግድ እና የኢንቬስትመንት ማዕቀፍ ስምምነት በ 2012 ዓም ተፈራርመዋል። ሚለር ማቶላ በውጭ ንግድ ላይ የተሰማራ « ብራንድ ሳውዝ አፍሪካ» የተባለው ተቋም ዋና ስራ አስኪያጅ ናቸው።
« የኦባማ የደቡብ አፍሪቃ ጉብኝት የሀገራችንን የኤኮኖሚ የወደፊት ዕድል እንዲያሻሽል ንእና ተጨማሪ ካፒታል ወደ ደቡብ አፍሪቃ እንዲመጣም እንፈልጋለን። በአሁኑ ጊዜ ዩኤስ አሜሪካ ዕቃ በንግድ ወደ ውጭ የምንልክባት ሁለተኛዋ ትልቋ ገበያችን ስትሆን፣ ወደ ሀገር በንግድ የምናስገባውን ዕቃ የምገዛባት በሦስተኛ ደረጃ የምትገኝ ሀገር ናት። ይህን ማሳደግ እንችላለን ብለን እናምናለን። እና ንግድን በተመለከተ ጉብኝቱ ለኛ ለደቡብ አፍሪቃውያን ብዙ ጥቅም ያስገኛል ብለን ተስፋ አድርገናል። »
ግን ሁሉ ደቡብ አፍሪቃውያን አይደሉም አሜሪካዊውን እንግዳ እጃቸውን ዘርግተው የሚቀበሉት። የሙሥሊም ጠበቆች ህብረት፣ በምሕፃሩ ለምሳሌ በሣምንቱ አጋማሽ በኦባማ ላይ በስብዕና አንፃር ወነጀል ፈፅመዋል በሚል የእስር ማዘዣ ለማውጣት ሞክሮ ነበር። ሙከራው ውድቅ ሆኖዋል። ህብረቱ ኤም ኤል ኤ ኦባማን በፓኪስታን እና በሶርያ ለ3000 ሰዎች ሞት ወይም መቁሰል ተጠያቂ አድርጓል። ይሁን እንጂ፣ ኤም ኤል ኤ በማህበራዊው የመገናኛ ዘርፍ ብዙ ወቀሳ ተፈራርቆበታል። የጆሀንስበርግ ዩኒቨርሲቲ ተማሪዎች እና መምህራን ለፕሬዚደንት ኦባማ የክብር ዶክትሬት ማዕረግ ለመስጠት በተያዘው ዕቅድ ላይ በወቅቱ ጠንካራ ክርክር ይዘዋል። አክራሪ ተማሪዎች ዕቅዱን በጥብቅ ተቃውመውታል።
የመገናኛ ብዙኃን ስለኦባማ ጉብኝት መነጋገር በያዙበት በዚሁ ጊዜ ግን በሰው ቤት ተቀጥራ የምትሰራው ፕሪቲ ናይሌያ ሀሳቧ በጠና ከታመሙት ማንዴላ ጋ ነው።
« በአሁኑ ጊዜ ትኩረታችን ያረፈው በማንዴላ ላይ ነው። ኦባማን ለማስተናገድ ጥቂት ጊዜ ብቻ ነው ያለን። ሀሳባችን ከማንዴላ ጋ ነው። ከዚህ በተረፈ ደግሞ ለአፍሪቃ ያን ያህል ፍላጎት ያላቸው አይመስለኝም። እርግጥ፣ ላንዳንድ አፍሪቃውያት ሀገራት ትኩረት ሰጥተዋል፣ ግን ሁሉም አይደሉም ከዚሁ ጥቅም የሚያገኙት። »
ሉድገር ሻዶምስኪ/አርያምተክሌ
መሥፍን መኮንን

Audios and videos on the topic

No comments:

Post a Comment