በ2012 ጋዜጠኞችን ማሰር ጨምርዋል ተባለ
የፊደል ቁመት 
ሄኖክ ሰማእግዜር
በዚህ በመገባደድ ላይ ባለው የአውሮፓዊያን ዓመት በታሪክ ቁጥራቸው ከመቼም ጊዜ የበለጠ ጋዜጠኞች የታሰሩበት ነው ሲል አንድ የጋዜጠኞች መብት ተሟጋች ቡድን ዛሬ አስታወቀ።

በኒውዮርክ መሰረቱን ያደረገው CPJ ይፋ ባደረገው ጥናት መሰረት ባለፉት 11 ወራት 232 ጸሃፊዎች፣ የፎቶ ጋዜጠኞች እና የህትመት አዘጋጆች ታስረዋል። ይሄም በ1996 ከተመዘገበው 185 ታሳሪዎች ቁጥር በእጅጉ የላቀ ሆኗል።

በዚህ መረጃ መሰረት የሲፒጄ የአፍሪካ ክፍል አስተባባሪ ሞሀመድ ኪታ ጋዜጠኞችን በማሰር በማያስመሰግን ደረጃ ስለሚገኙ አገሮች አብራርተዋል፡፡ በሞሀመድ አባባል በዓለም አቀፍ ደረጃ ኢራንን ተከትላ ቱርክ አንደኛ አሣሪ ሃገር ነች፡፡ ከዚያም ቻይና ትከተላለች፡፡ ከዚያም ኤርትራና ሦሪያ ይከተላሉ፡፡ እነዚህ አምስቱ ግንባር ቀደም ሃገሮች ናቸው፡፡ በርግጥ፣ ኢትዮጵያን፣ ኡዝቤክስታንን፣ ሳዑዲ አረቢያን፣ የመንን ጨምሮ ሌሎችም ሃገሮች እንዳሉ አብራርተዋል፡፡

ሞሀመድ እንዳሉት ሠሃራ በስተደቡብ ባለው አፍሪካ አርባ አራት ጋዜጠኞች ታሥረዋል፡፡ ከእነዚህ ውስጥ ሃያ ስምንቱን ያሠረችው ኤርትራ ነች፡፡ ኢትዮጵያ ውስጥ ስድስት ታሥረዋል፡፡ ኤርትራ ውስጥ የታሠሩት ጋዜጠኞች ተይዘው የሚገኙት ለወራትና ለዓመታት ያለክስና ያለፍርድ ነው፡፡

ምሥጢራዊ እሥር ቤቶች ውስጥ ገብተው አሁን ያሉበት አይታወቅም ሲሉ አስረድተዋል፡፡  አክለውም ኢትዮጵያ ውስጥ ያለውን ሁኔታ ያብራሩት ሞሀመድ ኢትዮጵያ ውስጥ መንግሥቱ ጋዜጠኞችንና ተቃዋሚዎችን ለማሠር በሽብር ፈጠራ ላይ የተከፈተውን ጦርነት እንደሽፋን ተጠቅሞበታል ይላሉ፡ እንደሳቸው አገላለፅ “የሽብር ሕግ” የሚለውን የብዥታ አጠራር ጋዜጠኞችንና ተቃዋሚዎችን በደፈናው ለመፈረጅ ጉዳይ አውሎታል፡፡